Page 3 - Ethiopia in the Bible by Abune Petros 2
P. 3
መግቢያ
ቀድሞ በዚህ በምንኖርበት በአሜሪካ ክርስቲያን ነን የሚሉ ሰባክያንና አማንያን የእግዚአብሔርን ቃል ሰዎችን ባሪያ
አድርጎ ለመግዛት ይጠቀሙበት ነበር የሚባለውን ሐሳብ ለመቀበል ረጅም ጊዜ ወስዶብኛል ። ምክንያቱም
ለእግዚአብሔር ቃል ያላቸውን ታማኝነት በኩራት የሚናገሩ ወንጌላውያን ፥ አብያተ ክርስቲያናት ፥ ሰባክያን ይህን
ይደፍራሉ ብየ በቀላሉ ስላላመንኩ ነበር ።
መጽሐፍ ቅዱስን የሁሉ ዳኛ አድርገን ስለምናቀርብ የቤተ ክርስቲያን መሪዎችንና ሐዋርያዊ ትውፊትን እንኳ ሳይቀር
ከመጽሐፍ ቅዱስ ጋር የሚስማማ መስሎ ካልታየን አንቀበልም እያሉ ሲምሉ ሲገዘቱ ስለምሰማ ነበር ። አሁን ላይ ሁኜ
ሳስብ ያ እምነቴ እውነትን የተከተለ አልነበረም ። ምክንያቱም ወንጌላውያን ነን የሚሉ ኢትዮጵያውያን ይህንኑ እያሉ
የእግዚአብሔር ቃል የሆነውን መጽሐፍ ቅዱስን ለዕለት ጥቅምና ፥ ለጎሣ ፖለቲካ ፍጆታ ብለው ሲደፍሩት ስላየሁ ነው ።
መቼም በጥላቻ የእግዚኣብሔርን ሐሳብ እንደ መለወጥ ያለ እርግማን የለም ። እግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ ቃሉን
በባሪያዎቹ በኩል ሲያስተላልፍ የሚጠቀምበት ሕዝብ የተለየ ሁኖ ሳይሆን እግዚብሔር ለዚያ ሕዝብም ሆነ ለጠቅላላው
ሕዝብ የሚያስተምርበት ስለ ሆነ ነው ። በዚህም ምክንያት እግዚብሔር ለቃሉ ታማኝ በመሆኑ ለፖለቲካ አጀንዳ ብሎ
ቅዱሳን ሰዎች በመንፈስ ቅዱስ ተነድተው የጻፉትን ቅዱስ ቃሉን ማረም በጣም ድፍረትም ኃጢአትም እርግማንም ጭምር
ነው ። (2 ጴጥ 1 ፥ 20-21) ።
የእግዚእብሔር ቃል ፣ ባሪያዎቹ በመንፈስ ቅዱስ ተነድተው ስለ ጻፉት የሰው ሐሳብ አለበት ብለን አናምንም ።
በመሆኑም እኛም አንጨምርም አንቀንስምም ፥ እንደ ተጻፈ እንጠቀማለን ። እግዚአብሔር እርሱ በመንፈስ እየመራ
ያጻፈውን መጽሐፍ መቀነስም መጨምርም እንደማይቻል በግልጥ ተነግሯል ። «እኔ የማዝዝህን ነገር ሁሉ ታደርገው ዘንድ
ጠብቅ ፤ ምንም በእርሱ ላይ አትጨምር ፥ ከእርሱም ምንም አታጕድል» (ዘዳ 4 ፥ 2) ።
የሐዲስ ኪዳኑ ጸሐፍት ይህንኑ ሐሳብ በተገቢ መልኩ በማስጠንቀቂያ መልክ ገልጸውታል «ይህን በመጀመሪያ እወቁ
፤ በመጽሐፍ ያለውን ትንቢት ሁሉ ማንም ለገዛ ራሱ ሊተረጉም አልተፈቀደም ፤ ትንቢት ከቶ በሰው ፈቃድ አልመጣምና ፥
ዳሩ ግን በእግዚአብሔር ተልከው ቅዱሳን ሰዎች በመንፈስ ቅዱስ ተነድተው ተናገሩ» (2ጴጥ 1 ፥ 20-21) ።
ይህን ውግዘት የሚያነብ ሰው ዐይነ ልቡናው ካልታወረ በቀር ለፖለቲካ ትርፍ ብሎ የተከበረውን የእግዚአብሔርን
ቃል በማቃለል ያርማል ብሎ ማሰብ ይከብዳል ።
የእግዚአብሔርን ቃል በተዛባ አእምሮ በመረዳት እንዲህ አይነት በደል መበደል ምን ይጠቅማል? እግዚአብሔር
ለቃሉ ስለሚጠነቀቅና ወደ መጨረሻው የሚመጡ ሰዎች ያልተላኩትን ተላክን ፥ ያላወቁትን አወቅን የሚሉትን ለማረም ።
የመጽሐፍ ቅዱስ መደምደሚያ የሆነው የዮሐንስ ራእይ እንዲህ በማለት ያስጠነቅቃል ። «በዚህ መጽሐፍ የተጻፈውን
የትንቢት ቃል ለሚሰማ ሁሉ እኔ እመሰክራለሁ ፤ ማንም በዚህ ላይ አንዳች ቢጨምር እግዚአብሔር በዚህ መጽሐፍ
የተጻፉትን መቅሠፍቶች ይጨምርበታል ፤ ማንምም በዚህ በትንቢት መጽሐፍ ከተጻፉት ቃሎች አንዳች ቢያጎድል ፥ በዚህ
መጽሐፍ ከተጻፉት ከሕይወት ዛፍና ከቅድስቲቱ ከተማ እግዚአብሔር ዕድሉን ያጎድልበታል» ይላል ። (ራእ. 22 ፥ 18) ።
እንግዲህ ከመተቸት አልፎ ቃሉን በድፍረት የሚሰርዝ ይህን እርግማን ሊሸከም ይችላል።
በመሠረቱ ኢትዮጵያውያን ይህን መብት ጠይቀው መንፈስ ቅዱስን አታልለው ስማችን በመጽሐፍ ቅዱስ ላይ
ይጻፍልን ብለው የጻፉት መጽሐፍ አይደለም ። እኛም ይህንን ጽሑፍ ለመጻፍ የተነሣንበት ዋና አላማ ለኢትዮጵያ ስም
ጥብቅና ቁመን በታላቁ መጽሐፍ የተጻፈውን የኢትዮጵያን ስም ለማስከበር አይደለም ። የተከበረውን መጽሐፍ ቅዱስ
በአግባቡ እንዲቀበሉ ለማረም ነው ።
“.ኢትዮጵያ እጆችዋን ወደ እግዚአብሔር ትዘረጋለች።” መዝሙረ ዳዊት - ም. 68 ቁ. 31 3