Page 5 - Ethiopia in the Bible by Abune Petros 2
P. 5
ዶ/ር በንቲም ሆነ የቤተ ክርስቲያናቸው የሥነ መለኮት ቅኝት ይህ ለዘብተኝነት ነው ። ይህ ሰዎችን ክርስቲያን
ከማድረግ ይልቅ ለሰዎች ፍላጎት የሚስማማ ክርስቶስን መፍጠር ዓላማው ያደረገን የሥነ መለኮት አካሄድ ነው ዶ/ር በንቲ
የፖለቲካ አጀንዳ ለማራመድ የሚጠቀሙበት ። ይህንኑ የተገለልን ትርክት ተከትለው ኢትዮጵያ የሚለው ቃል ጥቁር
ሕዝቦችን “ያገልላል ፥ ይሰድባል” የሚሉን ። ለምሳሌ ፦ የዶክትሬት ጥናታቸው (ለማስተርስ ከሠሩት ጥናት ያን ያህል
የሚለይ ሁኖ ባይታይም) የኦሮሞ ሕዝብ እምነት ከክርስትናና ከእስልምና በፊት የነበረ መሆኑን ማመዛዘንና ማወዳደር
የሚል ነው ።
“ከዚህ ፕሮጀክት ጀርባ ያለው ምክንያት ብዙ ክርስቲያን ሚሽነሪዎች ፤ ኢቫንጀሊካኖች እና ፓስተሮች የኦሮሞ ሕዝብ
ስለ እግዚአብሔር ሐሳቡ ፥ ዕውቀቱ የለውም እና ሃይማኖታቸውም በጣዖት ማምለክ ወይም በሰይጣን ማመን ነው ብለው
ይገምቱ ነበር ። በአካባቢ አህጉራችን የክርስትናና እስልምና ሃይማኖት ከመምጣቱ በፊት የነበረውን የኦሮሞን ሀገር በቀል
ሃይማኖት መመርመር መመልከት ጀመርኩ ። ስለዚህ ከሥነ መለኮት እይታ አኳያ የመመረቂያ ጽሑፌ የማነጻጸር
ሃይማኖታዊ ጥናት ነው ። እመለከት የነበረውም ነገር የኦሮሞ ነባር ሃይማኖት ከክርስትና ጋር ይጻረራል ወይስ ይስማማል
የሚለውን ነው” ።
ከዚህ በላይ ያለውን የዶክተር በንቲን ሐተታ ስንመለከተው ፣ የመመረቂያው ጽሑፋቸው የኦሮሞን ሕዝብ እምነትና
ባህል ፥ ከክርስትና ጋር በማወዳደር ላይ የተመሠረተ ነው ። በዚህ ከተመሠረተ ደግሞ ውጤቱ ያንኑ ለውድድር የቀረበውን
እምነት ከክርስትና ጋር ማወዳደር ይሆናል ። ይህ ማለት እውነተኛ የክርስትና እምነትና ሌላ የክርስትና የሚመስል ሐሳብ
ስለሚሆን የጠቅላላውን የመጽሐፍ ቅዱስንም ሆነ የጠቅላላ የሥነ መለኮትን አስተምህሮ ሐሳብ ሊይዝ ከቶ አይችልም ።
የመጽሐፍ ቅዱሱ የትርጉም ሥራ ውስጥ ሳይሳተፉ ራሳቸውን የተሳተፉ አስመስለው መቅረባቸውም የሰውየውን
ዓላማ በጥንቃቄ እንድናጤን ይጋብዘናል ። የጥንታዊ ጽሑፎች ሊቅ የሆኑት ፕሮፌሰር ጌታቸው ኃይሌ ይህን አስመልክቶ
የጻፉት ነገር ደምቆ ሊሠመርበት ይገባል ። ፕሮፌሰር እንዲህ ይላሉ ፦
“ጀርመኖች ማርቲን ሉተር መጽሐፍ ቅዱሱን ወደ ጀርመንኛ እስኪተረጕምላቸው ድረስ የሚጠቀሙት በላቲኑ ቅጂ
ነበር ። የተረጐመውም ሐዲሱን ከግሪክኛ ፥ ብሉዩን ከዕብራይስጥ ነበር ። በንቲ ስለ ጀርመንኛ መጽሐፍ ቅዱስ ብዙም
ስለማያውቅ ማርቲን ሉተር የተረጐመው ከላቲን ነው ይላል ። የጀርመን ቤተ ክርስቲያን አሁን ደግሞ መጽሐፍ ቅዱሷን
እንደ ገና ለ2017 ዓ.እ. እንዲደርስ አድርጋ ተርጕማለች ። የትርጐማው ግብረ ኀይል ሊቀ መንበር ፥ ፕሮፌሰር ዶክተር
ክሪስቶፍ ኬለር (Professor Dr.Christoph Kähler, Bishop Emeritus) በጽሑፍ እንደ ገለጠው ፥
ጀርመኖቹ መጽሐፍ ቅዱሳቸውን ትርጐማ ሲከልሱ ፥ ረቨረንድ በንቲ እንኳን የማርቲን ሉተርን አጽፍ ተጐናጽፎ በትርጐማ
ሊሳተፍ ቀርቶ ፥ አጠገባቸውም እንኳ አልነበረም” ።
ለነገሩ እንኳን ወደ ጀርመንኛ የሚሠራ ትርጉም ሥራ ላይ ለመሳተፍ ቀርቶ መጽሐፍ ቅዱስን ጀርመኖቹ ከምን ቋንቋ
እንደ ተረጎሙት እንኳ በትክክል የሚያውቁ አይመስልም ። ጀርመኖቹ ለብሉይ ኪዳን ዕብራይስጥን ፥ ለሐዲስ ኪዳን
ደግሞ ግሪክን በምንጭነት ተጠቅመዋል- ፕሮፌሰር ጌታቸው እንደ ጻፉት ። ዶ/ር በንቲ የሚነግሩን ግን ሉተር በ16ኛው
ክፍለ ዘመን ከላቲን ወደ ጀርመንኛ ስለ ተረጎመው መጽሐፍ ነው ። በዚያው ሉተር በሠራው ትርጉም ውስጥም ቢሆን
ጥቁር ሕዝብ የተጠራው የግሪኩን ወይም የላቲኑን ቅጂ መጽሐፍ ቅዱስ ተከትሎ “ኢትዮጵያ” ሲል አይገኝም ። ይልቁንም
የምናገኘው “Mohrenland” የሚል ነው ። ስለ ሆነም አዲሱ ትርጉም የበፊቱ ትርጉም Mohrenland ብሎ
ያቀረበውን የዕብራይስጡን ተከትሎ በማረም ወደ Kush ቀየረ እንጂ ሌላ ያደረገው ነገር የለም ። ዶ/ር በንቲ እዚህም
ላይ እውነተኝነት አይታይባቸውም ።
የቤተ ክርስቲያን አገልጋይ ነኝ ከሚል ፓስተር እንዲህ እውነትን እንዳናገኝ ያደረገበት ዋና ምክንያት ይኸው የጎሣ
ፖለቲካና ለዘብተኛ የሥነ መለኮት ቅኝት ነው ። ታዲያ በእነዚህ ሁለት ጭምብሎች ክርስቲያናዊ ማንነቱን ያጣ ሰው ቢዋሽ
ምን ይገርማል ! እውነትን ከሐሰት እንዳይለይ የእውነትን ቃል ተራ ቃል አድርጎታል ። የሰው ልጅ መሆንን እንዳያስቀድም
የጎሣ ፖለቲካ አእምሮውን አስሮታል ።
“.ኢትዮጵያ እጆችዋን ወደ እግዚአብሔር ትዘረጋለች።” መዝሙረ ዳዊት - ም. 68 ቁ. 31 5